እስከ ሚያዚያ 30 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ ሀብታቸውን ያላስመዘገቡ የተቋሙ ሠራተኞች ለቅጣት የሚዳረጉ መሆኑን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የሥነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና መከታትያ መምሪያ ገለጸ።
በመምሪያው የሙስና ተጋላጭነትና ሥልጠና ሥራ አስኪያጅ አቶ መንግሥቱ አባይነህ እንደገለጹት በሀብት ማሳወቂያና ማስመዝገቢያ አዋጅ ቁጥር 668/2002 መሠረት ሁሉም የተቋሙ ሠራተኞችና የሥራ መሪዎች ሀብታቸውን የማስመዝገብ ግዴታ አለባቸው።
ሠራተኛው የራሱን እና የትዳር ጓደኛውን እንዲሁም ከ18 ዓመት በታች የሆነ ልጁን ጨምሮ ቋሚና ተንቀሳቃሽ ንብረት፣ የገቢ ምንጭና ዕዳ ማስመዝገብ ይኖርበታል ብለዋል።
ሆኖም በውርስ የተገኘ የጋራ ንብረት፣ የቤት ዕቃዎች፣ የግል መገልገያዎችና የጡረታ ገቢ በአዋጁ ከምዝገባ ነጻ መሆናቸውን አብራርተዋል።
አዋጁን መሠረት በማድረግ ሁሉም ሠራተኛ ማስመዝገብ ያለበት ቢሆንም መምሪያው ለአሠራር እንዲያመች በተቋሙ ከPR 1 የሥራ መደብ በላይ ያሉ ሠራተኞች ሀብታቸውን እስከ ሚያዚያ 30 ቀን እንዲያስመዘግቡ አቅጣጫ አስቀምጦ እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
ምዝገባው የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ከኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ጋር በመተባበር በበለፀገው ሶፍትዌር የሚከናወን በመሆኑ መምሪያው እስከ አሁን ከ1 ሺህ 243 ሠራተኞች ውስጥ 982 ሠራተኞችን ከሲስተሙ ጋር የማገናኘት ሥራ ማከናወኑን ጠቁመዋል።
ሆኖም እስከ አሁን በሲስተሙ ገብተው ሀብታቸውን አስመዝግበው ሠርተፍኬት የወሠዱ ሠራተኞች 304 ብቻ መሆናቸውን ተናግረዋል።
የተቋሙ ሠራተኞች ከሚያዘያ 30 ቀን 2018 ዓ.ም በፊት ምዝገባውን ካላከናወኑ በኮሚሽኑ አንድ ሺህ ብር ተቀጥተው ሀብታቸውን እስከሚያስመዘግቡ ድረስ ደመወዛቸው እንደሚታገድ አብራርተዋል።
የሀብት ምዝገባው ላይ የሚኖረው ተሳትፎ በተቋሙ ገጽታ ላይ አስተዋጽኦ እንዳለው በመረዳት በቀሪ ጊዜያት ሁሉም የሥራ መሪዎችና ሠራተኞች የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡