የግድቡ መጠናቀቅ ባለመጨረስ የባሕል ልምምድ ላይ የተሰነዘረ መዶሻ ነው

የግድቡ መጠናቀቅ ባለመጨረስ የባሕል ልምምድ ላይ የተሰነዘረ መዶሻ ነው

‎የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ተጠናቆ ለምርቃት ዝግጁ መሆን ትልልቅ ፕሮጀክቶችን ጀምሮ ያለመጨረስ የባሕል ልምምድ ላይ የተሰነዘረ መዶሻ መሆኑን የአፍሪካ ሥራ አመራር አካዳሚ ፕሬዝዳንት ዛዲግ አብርሃ ተናገሩ።

‎ፕሬዚደንቱ ይህን የተናገሩት ለሕዳሴ ግድብ ምክር ቤት ከፍተኛ አመራሮች እና ባለሙያዎች  በሰጡት ስልጠና ላይ ነው።

‎እንደ አቶ ዛዲግ ገለጻ ታላቁ የህዳሴ ግድብ ፉክክርን ወደ ትብብር በመቀየር ትልልቅ ፕሮጀክቶችን ጀምሮ የመፈጸም ሀገራዊ መሰረት የተጣለበት እንዲሁም ብሔራዊ ማንነታችንንና የፍላጎታችንን አዋጅ የተነገረበት ነጋሪት ጋዜጣ ነው።

‎የግድብ ግንባታው የመሰረት ድንጋይ ሲቀመጥ ቦንድ የገዛውና ገንዘብ የለገሰው ሕዝብ በወቅቱ ይታየው የነበረው የመሰረት ድንጋይ ሳይሆን የመነጨ የኤሌክትሪክ ኃይል እና ብርሃን ነበር ብለዋል።

‎ሕዝቡ ከመንግስት ጋር በመተባበር በጨለማ እየኖረ በቅርብ ላላየው ብርሃን ታጋይ ሆኖ የዘመኑ አደዋ የሆነውን የሕዳሴ ግድብ ግንባታን የማጠናቀቂያ ምዕራፍ ላይ እንዲደርስ ማድረጉን ገልጸዋል።

‎የፕሮጀክቱ የግንባታ ሥራ መጠናቀቅ የአባይ ምንጭ የነበረችዋን ኢትዮጵያ 5 ሺ 150 ሜጋ ዋት ኃይል በማመንጨት የአፍሪካ የታዳሽ ኃይል ማዕከል እንድትሆን መደላድል የሚፈጥር መሆኑን አብራርተዋል።

‎እንደ አቶ ዛዲግ ገለፃ ግድቡ አፍሪካ ያላትን ፀጋ በራሷ ልጆች ዕውቀት፣ ጉልበትና ገንዘብ ወደ ሀብት በመቀየር መልማት እንደምትችል ለዓለም ያሳየ የአደባባይ ትዕምርት ነው።

? “ንፁህ ኢነርጂ ለተሻለ ህይወት!”

Scroll to Top