የጊቤ ግድቦች ኢትዮጵያ የውሃ ሀብቷን በአግባቡ መጠቀም የመጀመሯ ማሳያ ናቸው – ዛዲግ አብርሃ

የጊቤ ግድቦች ኢትዮጵያ የውሃ ሀብቷን በአግባቡ መጠቀም የመጀመሯ ማሳያ ናቸው – ዛዲግ አብርሃ

‎በኦሞ ጊቤ ተፋሰስ ላይ የተገነቡት የግልገል ጊቤ 1 እና 2 እንዲሁም የጊቤ 3 የውሃ ኃይል ማመንጫ ግድቦች ኢትዮጵያ የውሃ ሀብቷን በአግባቡ መጠቀም የመጀመሯ ማሳያ መሆናቸውን የአፍሪካ አመራረረ ሥራ አመራር አካዳሚ ፕሬዝዳንት ዛዲግ አብርሃ ገለጹ።

‎እንደ ፕሬዝዳንቱ ገለጻ ይህ የግቤ ሰንሰለት የኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይልና የኢኮኖሚ ከፍታ ማሳያ ከመሆኑም በተጨማሪ የቀጠናው የኃይል ማማ እንድትሆን አስችሏታል።

‎ እ.ኤ.አ በ2004 ሥራ የጀመረው የግልገል ግቤ 1፣ 184 ሜጋ ዋት በማመንጨት በወቅቱ የነበረውን የኃይል እጥረት በመቅረፍ ለሀገሪቱ የኢንዱስትሪ መነሳሳት መሠረት እንደነበር አስታውሰዋል።

‎ይህ ግንባር ቀደም ፕሮጀክት የኦሞ ወንዝን ያልተገራ ኃይል ለመጀመሪያ ጊዜ ለታላቅ ሀገራዊ ዓላማ ያዋለ ታሪካዊ ስኬት መሆኑንም አብራርተዋል።

‎እንደ አቶ ዛዲግ ገለጻ የዘመኑን የኢንጅነሪንግ ቴክኒዮሎጅ የተገለጠበት የግልገል ጊቤ 2 ማመንጫ ትልቅ የውኃ ማጠራቀሚያ ሳይኖረው ከግልገል ግቤ 1 የወጣውን ውኃ በ26 ኪሎ ሜትር ርዝመት ባለው የተራራ ውስጥ ዋሻ አሳልፎ ቁልቁል በመጣል 420 ሜጋ ዋት ኃይል ያመነጫል።

‎ተጨማሪ ወንዝ ሳይገደብ በአንድ ወንዝ ላይ የተሠራውን ውሃ በድጋሚ በመጠቀም ኃይል ማመንጨቱ የኢትዮጵያ ምሁራንና መሐንዲሶች ያሳዩት የብልሃትና የጥበብ ሥራ ትልቅ ማሳያ ተደርጎ የሚወሰድ መሆኑንም ጠቁመዋል።

‎ከታላቁ የህዳሴ ግድብ ቀጥሎ የሀገሪቱን የኃይል አቅርቦት ወደ ላቀ ደረጃ ያሸጋገረው ግዙፉ ግቤ 3 ደግሞ 1 ሺህ 870 ሜጋ ዋት የማመንጨት አቅም ያለው የሀገር ኢኮኖሚ ዋልታ መሆኑን አስገንዝበዋል።

‎ግድቡ ሥራ በጀመረበት ወቅት የሀገሪቱን አጠቃላይ የኃይል አቅርቦት በአንድ ጊዜ በእጥፍ ማሳደጉን ያወሱት ፕሬዝዳንቱ ግድቡ በግንባታው ወቅት በ243 ሜትር በአፍሪካ ረጅሙ ግድብ ተብሎ መመዝገቡ ጠቁመዋል።

‎በአሁኑ ወቅት ለኬንያ፣ ለጂቡቲ እና ለሱዳን የሚሸጠው የኤሌክትሪክ ኃይል ዋነኛው ምንጭ ግቤ 3 በመሆኑ ለሀገሪቱ በየዓመቱ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ በማስገኘት በኩል የማይተካ ሚና እየተጫወተ ይገኛልም ብለዋል።

‎ሦስቱ ኃይል ማመንጫዎች ውኃን በቁጠባና በከፍተኛ ብቃት ለመጠቀም የሚያስችል ሥርዓት በኢትዮጵያ ያስተዋወቁ መሆናቸውን አብራርተዋል።

‎በተጨማሪም የኦሞ ወንዝ በየዓመቱ የሚያደርሰውን የጎርፍ አደጋ በመቀነስ የታችኛው የኦሞ ሸለቆ ነዋሪዎች በተረጋጋ ሁኔታ እንዲኖሩና በመስኖ ልማት እንዲሰማሩ ዕድል መፍጠራቸውንም ገልጸዋል።

‎በቀጣይ ጊዜ ግቤ 4 እና ግቤ 5 ሲገነቡ የኦሞ ወንዝ ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለመላው ምሥራቅ አፍሪካ የኃይል ዋስትና መሆኑ የማይካድ ሃቅ መሆኑንም አስገንዝበዋል።

‎የግቤ የግድቦች ሰንሰለት ኢትዮጵያ የተፈጥሮ ሀብቷን በቴክኖሎጂ ታግዛ ወደ ብርሃን፣ ወደ ኢንዱስትሪና ወደ ኢኮኖሚ ከፍታ የለወጠችበት የታላቅነት ምስክር ነው መሆኑንም አብራርተዋል።

‎እያንዳንዱ ሜጋ ዋት ለኢንዱስትሪ ዕድገት አዲስ ተስፋ የሚሰጥ ሲሆን ውኃ የኢትዮጵያ ነዳጅ መሆኑን በተግባር ያረጋገጡ ፕሮጀክቶች መሆናቸውን አቶ ዛዲግ አስገንዝበዋል።

Scroll to Top