ፓርቲው ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ የገንዘብ ድጋፍ አደረገ

የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ( ኢዜማ) ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ የግማሽ ሚሊዮን ብር ስጦታ አበረከተ።
በድጋፍ ፕሮግራሙ ላይ የተገኙት የፓርቲው መሪ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ በልዩነት ብቻ የተመሰረተውን የኢትዮጵያ ፖለቲካ በማሻሻል በጋራ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ በትብብር መሥራት ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
ፓርቲው ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ያደረገው ድጋፍም የትብብሩ አንዱ ማሳያ ነው ብለዋል።
ፕሮፌሰር ብርሃኑ እንዳሉት ስጦታው በሀገር ውስጥና በሀገር ውጭ ከሚኖሩ የፓርቲው አባላት ለዚሁ ዓላማ የተሰበሰበ ነው፡፡
ኢትዮጵያውያን ባለፈው ታሪካችው በሀገራዊ የጋራ አጀንዳዎች ላይ የማይደራደሩ መሆናቸውን አስታውሰው ሁሉም ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች በልዩነት ምክንያት ሀገራዊ ጥቅማቸውን ለአፍታም ቢሆን አሳልፈው መስጠት እንደሌለባቸው አሳስበዋል፡፡
ኢዜማ በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የማያወላውል አቋም እንዳለውና ወደፊትም ድጋፉን እንደሚቀጥል ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ አረጋግጠዋል፡፡
የታላቁ ህዳሴ ግድብ ህዝባዊ ተሳትፎ ብራሄራዊ ማስተባበሪያ ምክር ቤት ጽ/ቤት ምክትል ዳይሬክተር አቶ ታገል ቀኑብህ በበኩላቸው ኢዜማ ያደረገው ድጋፍ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች በጋራ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ አንድ መሆን እንዳለባቸው ማሳያ ነው ብለዋል፡፡
ከአሁን በፊት ፓርቲዎች በእንደዚህ ዓይነት ሀገራዊ ልማት ላይ የሚያሳዩት ተሳትፎ ብዙም እንዳልነበር አቶ ታገል ጠቁመዋል፡፡ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ነገ መንግሥት ሆነው ቢመረጡ የሚያስተዳድሩት አሁን በልዩነት ሁነው የሚሰሩትን መልካም ሥራ በመሆኑ በጋራ ሀገራዊ ጉዳይ ላይ የጋራ ኃላፊነት እንዳለባቸው ሊገነዘቡ ይገባል ብለዋል፡፡
0 Comments