ዶ/ር አብርሃም በላይ የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ሆነው ተሾሙ

Published by corporate communication on

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ስራ አስፈፃሚ ሆነው ከነሐሴ 2010 ዓ.ም ጀምሮ ያገለገሉት ዶ/ር አብርሃም በላይ የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ሆነው ተሾሙ፡፡

ዶ/ር አብርሃም ተቋሙን በመሩባቸው ጊዜያት የተቋማዊ ለውጥ ስራዎችን በማቀድና በመምራት ተቋሙን ወደ ተሻለ ደረጃ ማሸጋገር ችለዋል፡፡

ከነበረበት የእዳ ጫና የሚያላቅቅ የብድር ማስተካከያ እንዲደረግና የተቋሙ ያልሆኑ ብድሮች ወደ ሚመለከታቸው አካላት እንዲተላለፉ ትልቅ ስራ ሰርተዋል፡፡

ለዓመታት በካሳ ክፍያ የተነሳ ሲጓተት የነበረውን የገናሌ ዳዋ 3 ፕሮጀክት ተጠናቆ ለምርቃት ዝግጁ እንዲሆን፣ የኮይሻ የውሃ ኃይል ማመንጫ እና የአይሻ የንፋስ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶች መልካም አፈፃፀም እንዲኖራቸውና ሰራተኛው በተቋሙ ላይ ያለው የእኔነት ስሜት እንዲያድግ ማድረግ ችለዋል፡፡

የታላቁ ህዳሴ ግድብም ወደ ትክክለኛ መስመር እንዲመለስ ያደረጉ፣ በፕሮጀክቱ ሳይት ላይ ቢያንስ በወር አንድ ጊዜ በመገኘት አፈፃፀሙን በመከታተል ድጋፍና ክትትል ያደረጉ ኃላፊ ናቸው፡፡

ተቋሙ በኮርፓሬት ቢዝነስ አስተሳሰብ እንዲመራ በማድረግ የ5 አመት ስትራቴጂ እንዲቀረፅም አድርገዋል፡፡

ለረዥም አመታት በጥገና ቆመው የነበሩ የኃይል ማመንጫ ዩኒቶች ወደ ሀይል እንዲመለሱና በዘላቂነት የመለዋወጫ አቅርቦት መፍትሄ እንዲያገኝ የማዕቀፍ ስምምነት ስርዓት እንዲዘረጋ አድርገዋል::

በተጨማሪም አዳዲስ የገቢ ማስገኛ ስልቶችን በመቀየስ የተቋሙን የፋይናንስ አቅም ወደ ጤነኛ አቋም የሚመልሱ ስራዎችን፣  የደመወዝ ማሻሻያ፣ የግሬድማስተካከያ፣  የጥቅማጥቅም ማሻሻያ ስራዎች በተቋሙ ከሰሯቸው ስራዎች መካከል ይጠቀሳሉ፡፡

ዶ/ር አብርሃም በላይ በሄዱበት ቦታ ስኬት እንዲገጥማቸው መላው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ሰራተኛ እና ማኔጅመንት ይመኛል፡፡

 

Categories: ዜና

0 Comments

Leave a Reply

Avatar placeholder

Your email address will not be published.

nineteen − 3 =