የሻሸመኔ የኃይል ማከፋፈያ ጣቢያ የአቅም ማሳደግና የማሻሻያ ሥራ ተጠናቀቀ

Published by corporate communication on

የሻሸመኔ የኃይል ማከፋፈያ ጣቢያ የአቅም ማሳደግና የማሻሻያ ሥራ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት መጀመሩን በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የደቡብ ሪጅን የኃይል ማስተላለፊያ እና ማከፋፊያ ጣቢያ ቢሮ አስታወቀ፡፡

የኃይል ማከፋፈያ ጣቢያው ከሠላሳ ዓመታት በላይ ለሻሸመኔ ከተማና አጎራባች ወረዳዎች አገልግሎት እየሰጠ ቢቆይም በየጊዜው እያደገ የመጣውን የህብረተሰቡን የኃይል ፍላጎት ጥያቄ ማስተናገድ እንዳልቻለ ሪጅኑ ጠቁሟል፡፡

25 ሜጋ ቮልት አምፒር የመሸከም አቅም በነበረው አንድ ትራንስፎርመር ለከተማውና አጎራባች አካባቢዎች ኃይል ለማዳረስ ጥረት ሲደረግ ቢቆይም ፍላጎቱ ከጣቢያው አቅም በላይ ሆኖ ቆይቷል፡፡

ይህም በሻሸመኔ ከተማ እና አጎራባች ወረዳዎች ኤሌክትሪክ በፈረቃ እንዲሰጥ በማድረግ  በህብረተሰቡ ዘንድ ከፍተኛ ቅሬታ አሳድሮ እንደነበር ሪጅኑ ገልጿል፡፡

ጣቢያው ያለበትን ችግር ለመቅረፍ በተሰራው ሥራ 50 ሜጋ ቮልት አምፒር መሸከም የሚችል የኃይል ትራንስፎርመር በመትከልና የተለያዩ የማሻሻያ ሥራዎችን በማከናወን አቅሙን በእጥፍ ለማሳደግ እንደተቻለ አስታውቋል፡፡

15 ኪሎ ቮልት አቅም ያላቸው 6 ወጪ መስመሮችን አቅም የማሳደግ፣ የመቆጣጠሪያና የመከላከያ መሳሪያዎችን በአዲስ መልክ የመትከል ሥራዎችም ተከናውነዋል፡፡

ለማስፋፊያ እና ማሻሻያ ሥራው ከ1 ነጥብ 4 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በማድረግ የህብረተሰቡን የረጅም ጊዜ የኃይል ፍላጎት ጥያቄ ምላሽ መስጠት መቻሉን ሪጅኑ ገልጿል፡፡

Categories: ዜና

0 Comments

Leave a Reply

Avatar placeholder

Your email address will not be published.

3 + five =