አስተማማኝ የኤሌክትሪክ ኃይል ለማምረት በትኩረት እየሰራ ነው፡፡

Published by corporate communication on

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል በ2012 በጀት ዓመት አስተማማኝ የኤሌክትሪክ ኃይል ለማምረት በኦፕሬሽን፣ ጥገናና ኢንስፔክሽን ሥራዎች ላይ ትኩረት ተሰጥቶት እየሰራ መሆኑን አስታወቀ፡፡


በተቋሙ የኃይል ማመንጫዎች ኦፕሬሽን ሥራ አስፈፃሚ አቶ አንዳርጌ እሸቴ እንደገለፁት በበጀት ዓመቱ 16,446.85 ጊጋ ዋት ሰዓት ለማምረት እቅድ ተይዟል፡፡


የተያዘውን እቅድ ለማሳካት በጣቢያዎች ላይ የኦፕሬሽን.፣ ጥገናና ኢንስፔክሽን ስራዎች በእቅድ እንዲከናወኑ ክትትል እየተደረገ መሆኑን ገልጧል፡፡


በጣቢያዎች ላይ የሚከሰቱ ድንገተኛ የቴክኒካል ችግሮችን ለመፍታትና ኃይል የማመንጨት ስራን አስተማማኝ ለማድረግ የቴክኒካል ድጋፍ ሰጪ ቡድን ተቋቁሞ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡ 


እንደ ሥራ አስፈፃሚዉ ገለፃ አስተማማኝ ኃይል ለማመንጨት እንዲቻል በመለዋወጫ እቃዎች ችግር ምክንያት የጥገና ስራ ማከናወን ባልተቻለባቸው ማመንጫ ጣቢያዎች የመለዋወጫ እቃዎች እንዲቀርቡ ከተለያዩ ኩባንያዎች ጋር የማዕቀፍ ግዢ ስምምነት ተፈርሟል፡፡


ለአንዳንድ ጣቢያዎችም የተገዙት እቃዎች ወደ ሃገር ውስጥ በመግባት ላይ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡ 


አቶ አንዳርጌ እንዳሉት በ2011 በጀት ዓመት በግድቦች ላይ ተከስቶ የነበረው የውሃ እጥረት በተያዘው በጀት ዓመት እንዳይደገም፤ ወደ ኃይል ማመንጫ ጣቢያ ግድቦች የሚገባውን ውሃ ቆጥቦ ለመጠቀም የሚያስችል አዲስ የውሃ አጠቃቀም ስርዓት ጥናት (reservoir water management) ተከናውኗል፡፡ ጥናቱን ለመተግበርም ዝግጅት እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡


ግድቦች ያጠራቀሙትን ዉሃ ቆጥበው እንዲጠቀሙ ለማድረግ በየጣቢያዎች “Zero Spillage” መኖሩን የሚከታተል ቁልፍ የአፈፃጠም መለኪያ “KPI” በማስቀመጥ ያለ አግባብ የሚፈሰውን ውሃ የመከታተል ሥራ እየተሰራ መሆኑንም ነው አቶ አንዳርጌ የገለጹት፡፡


ግድቦች ይይዛሉ ተብሎ የታሰበውን ውሃ በሙሉ አቅማቸው እንዲይዙ ለማድረግ ግድቦችን ከደለል መከላከል ያስፈልጋል ያሉት ሥራ አስፈፃሚው የደለል መጠን መለኪያ መሳሪያ (Eco Sounding Instrument) ግዥ በማከናወን (Bathymetric Measurement) በግድቦች የውሃ ማጠራቀሚያ አካላት ላይ ለመትከል እንቅስቃሴ መጀመሩን አስታውቀዋል፡፡


በግድቦች አካባቢ ከሚኖሩ የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር መልካም ግንኙነት እንዲኖር ለማድረግ በተለያየ ጊዜ የሚያነሷቸውን የልማት ጥያቄዎችን ለመመለስ ጥረት እየተደረገ መሆኑን አቶ አንዳርጌ ጠቁመዋል፡፡

ህዳር 15/2012 ዓ.ም.

Categories: ዜና

0 Comments

Leave a Reply

Avatar placeholder

Your email address will not be published.

sixteen + eight =