ተቋሙን በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ለማዘመን ዘርፈ ብዙ ሥራዎች መከናወናቸው ተገለፀ

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል በበጀት ዓመቱ 6 ወራት ውስጥ ተቋሙን በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጅ ለማዘመን ዘርፈ ብዙ ሥራዎችን ማከናወኑ አስታወቀ፡፡
የተቋሙ የአይሲቲ መሠረተ ልማት ሥራ አስኪያጅ ወ/ሮ ጽዮን በቀለ እንደገለፁት በ6 ወራት ውስጥ ተቋሙ የሚጠቀምባቸውን የአይሲቲ አውታረ መረብ መሰረተ ልማትና የዳታ ማዕከል መቋረጥን በመቀነስ ተደራሽነቱን የማሻሻል ሥራ ተሰርቷል፡፡
የሥራ ክፍሉ ለብሔራዊ የኃይል መቆጣጠሪያ ማዕከል የመስመር ላይ የኃይል መቋረጥ (online Power interruption) መከታተያ እና መጠየቂያ ሲስተም በኦንላይን ማስተናገድ የሚያስችሉ ሦስት ሶፍትዌሮችን እንዳበለፀገ ወ/ሮ ጽዮን ገልፀዋል፡፡
በተቋሙ ያሉ የሥራ ክፍሎችን እና የሪጅን ቢሮዎችን ከዳታ ማዕከል ጋር የማገናኘት፣ የአውታረ መረብና ዋይ ፋይ መሰረተ ልማት የመዘርጋት እና ለተቋሙ የIT ተጠቃሚ ደንበኞች ጥራት ያለው ድጋፍና የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ አገልግሎት ለመስጠት የድጋፍ ማዕከል (Help Desk) የማቋቋም ሥራ መከናወኑን አስታውቀዋል፡፡
በቀጣይም የኃይል ማመንጫዎችንና የሪጅን ቢሮዎችን ከዳታ ማዕከሉ ጋር የማገናኘት፣ ሁሉንም የድርጅቱ ቢሮዎች የአውታረ መረብ መሰረተ ልማት ተደራሽ የማድረግ እና የSAP ሲስተምን መጠቀም እንዲችሉ የማድረግ ሥራዎች እንደሚከናወኑ ሥራ አስኪያጇ ጠቁመዋል፡፡
0 Comments