በዋና ሥራ አስፈፃሚው የተመራ የተቋሙ ከፍተኛ የስራ አመራር ቡድን የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታን ጎበኘ

Published by corporate communication on

በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ አሸብር ባልቻ የተመራ የተቋሙ ከፍተኛ የስራ አመራር ቡድን የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታን ጎብኝቷል።

የግድቡ ግንባታ አሁን የደረሰበትን ደረጃ፣ ቀሪ ግንባታውን ለማፋጠንና ለሁለተኛው ዙር የውሃ ሙሌት እየተሰሩ ያሉት ወሳኝ ስራዎችን በተመለከተ በግድቡ ግንባታ ምክትል ስራ አስኪያጅ ኢ/ ር ኤፍሬም ገ/ኪዳን ማብራሪያ ተሰጥቷቸዋል።

የዋናውን ግድብ ፣ የኮርቻ ቅርፅ ግድቡን የኃይልማመንጫ ቤቱንና ውሃው በግድቡ ላይ የሚፈስበትን ስፍራ ቡድኑ ተዘዋውሮ ጎብኝቷል።

የስራ አመራር ቡድኑ ጉብኝት ዋና ዓላማ በመጀመሪያ ዙር የውሃ መሊት የተመዘገበውን ስኬት በስፍራው በመገኘት ለመመልከትና የፕሮጀክት አስተዳደሩን ለማገዝ ነው።

ይህን መሰል ጉብኝት መዘጋጀቱ የሥራ አመራሩ ፕሮጀክቶችን በቅርበት በመመልከት አስፈላጊውን ክትትልና ድጋፍ ለመስጠት እንደሚያግዘው ታምኖበታል።

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የስራ አመራር ቡድን የታላቁ ኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ፕሮጀክትን በጋራ ሲጎበኝ የአሁኑ የመጀመሪያው ነው።

የግድቡ አጠቃላይ ግንባታ በአሁኑ ወቅት 76 ነጥብ 3 በመቶ ደርሷል።

በተያያዘ ዜና የስራ አመራር ቡድኑ በገበታ ለሀገር ፕሮጀክት የተካተተውንና በኮይሻ በመገንባት ላይ የሚገኘውን የኮይሻ የውሃ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክትንም ጎብኝቷል።

Categories: ዜና

0 Comments

Leave a Reply

Avatar placeholder

Your email address will not be published.

six − one =