በተቋሙ ዘመናዊ የሆነ ተንቀሳቃሽ ወይም ሞጁላር (Modular) ዳታ ማዕከል ተገነባ

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አሰራሩን ለማዘመንና ውጤታማ ለማድረግ የሚያግዝ ዘመናዊ የሆነ ተንቀሳቃሽ ወይም ሞጁላር (Modular) ዳታ ማዕከል መገንባቱን ገለፀ፡፡
የተቋሙ የአይሲቲ መሠረተ ልማት ሥራ አስኪያጅ ወ/ሮ ጽዮን በቀለ እንደገለፁት የዳታ ማዕከሉ መገንባት ለድርጅቱ ወሳኝ የሆኑትን የመረጃ ሥርዓቶች ደህንነቱ በተጠበቀ ሁኔታ ለማስቀመጥ፣ በቀላሉ ለመጠቀም፣ ለማስተዳደር እና ለመቆጣጠር ያስችላል፡፡
እንደ ወ/ሮ ጽዮን ገለጻ ዳታ ማዕከሉ የሰርቨር፣ የኤሌክትሪክ ገቢ ዋና የስርጭት ቦርድ እና የማዕከሉን የመቆጣጠሪያ ክፍሎችን ያየዘ ሲሆን የማዕከሉን ደህንነት ለመጠበቅ የበር መቆጣጠሪያ (Door Access Control System) ተገጥሞለታል፡፡
ለማዕከሉ ደህንነት አጋዥ የሆኑ 16 ካሜራዎች እንደተገጠሙለትና የዳታ ማዕከሉን ዕቃዎች ለመቆጣጠር የሚያስችል Data center Infrastrucutre Manager የሚባል ሲስተም መተግበሩን ሥራ አስኪያጇ አብራርተዋል፡፡
ሰርቨሮች የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ እንዳይገጥማቸው ጀነሬተር እና ዩ ፒ ኤስ እንደተገጠመላቸውና የዳታ ማዕከሉን ለመቆጣጠር የሚያስችሉ የማቀዝቀዣ (cooling system)፣ የሙቀት፣ የጭስ እና የውሃ ፍሳሽ መቆጣጠሪያ ሴንሰሮች የተገጠመለት ዘመናዊ ማዕከል መሆኑ ተገልጿል፡፡
የማዕከሉን ግንባታ ISYX TECHNOLOGIES L.L.C በሚባል የውጭ ሃገር ኩባንያ ነው፡፡ ማዕከሉን ሰርቶ ለማጠናቀቅ 173 ነጥብ 7 ሚሊዮን ብር የወጣ ሲሆን የተሽፈነውም በተቋሙ በጀት ነው፡፡
0 Comments