በስማርት ሜትር ቆጣሪ አጠቃቀም ዙሪያ ስልጠና በመሰጠት ላይ ነው

ከኢትየጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ከተለያዩ የስራ ክፍሎች ለተውጣጡ ሠራተኞች በስማርት ሜትር ቆጣሪ አጠቃቀም ዙሪያ ላይ ያተኮረ ስልጠና በመሰጠት ላይ ይገኛል፡፡
ስልጠናው በማከፋፈያ ጣቢያዎች ላይ የተተከሉትን ስማርት ሜትሮች አገልግሎት ላይ ለማዋል እና እንዴት መጠቀም እንደሚቻል እንደሚረዳ በተቋሙ የስማርት ሜትር ፕሮጀክት ሥራ አስኪያጅ ወ/ሮ ሃይማኖት ተፈራ ገልፀዋል፡፡
ስልጠናው ስማርት ሜትሮች እንዴት መጠቀም እንደሚቻል፣ የቆጣሪ ንባብ እንዴትና መቼ መውሰድ እንደሚቻል፣ ቢል እንዴት መስራትና መውሰድ እንደሚቻል፣ ከሜትሮች ጋር አብሮ የመጣውን ሶፍትዌር እንዴት መሞላት (configure) መደረግ እንዳለበት፣ በስማርት ሜትሩ ላይ ያሉ መመሪያዎችን (parameters) እንዴት ማስተካከል እና መሙላት (configure) እንደሚቻል እንዲሁም ኢነርጂ ሜትሮች እንዴት መስራት (install) መደረግ እንዳለባቸው በሚሉ ጉዳዮች ላይ ትኩረት እንደሚያደርግ ሥራ አስኪያጇ ተናግረዋል፡፡
በስልጠናው ላይ ከጀኔሬሽን ኦፕሬሽን፣ ከትራንስሚሽንና ሰብስቴሽን ኦፕሬሽን ሪጅኖች፣ ከኤል ዲ ሲ (load dispatch center) ከማርኬቲንግና ቢዝነስ ልማት መምሪያ፣ ከኤሲቲ፣ ከሳይበር ሴኩሪቲ እና ከኢንጅነሪንግ የስራ ክፍሎች የተውጣጡ 39 ባለሙያዎች በመሳተፍ ላይ እንደሚገኙም ወ/ሮ ሃይማኖት ጠቁመዋል፡፡
ሠራተኞች ከስልጠናው ያገኙትን ዕውቀት ወደ ሥራ ገበታቸው ሲመለሱ በተግባር ላይ ማዋል እና ለሌሎች የስራ ባልደረቦቻቸው ግንዛቤ መፍጠር እንዳለባቸው ኃላፊዋ አሳስበዋል፡፡
የስልጠናው ተሳታፊዎች በበኩላቸው የስማርት ሜትር ቴክኖሎጂ አዲስ በመሆኑ ስልጠናው ቴክኖሎጂውን በመረዳት ሥራቸውን በቀላሉና በአጭር ጊዜ ለማከናወን ዕድል እንደሚፈጥርላቸው ተናግረዋል፡፡
ስልጠናው ከመስከረም 24 እስከ ጥቅምት 2 ቀን 2014 ዓ.ም ድረስ የሚቆይ ሲሆን በማከፋፈያ ጣቢያዎች ላይ የስማርት ሜትር ቆጣሪዎችን የገጠማ ስራ ባከናወነው “Siemens Proprietary Limited” በተሰኘ ኩባንያ አማካኝነት እየተሰጠ ነው፡፡
0 Comments