በሪጅኑ የኃይል ፍላጎት ጥያቄ እየጨመረ ቢመጣም እያስተናገድኩ ነው – ሪጅኑ

Published by corporate communication on

የከተሞች መስፋፋት፣ የህዝብ ቁጥር ዕድገትና የኢንዱስትሪ ፍሰት ያመጣውን የኃይል ፍላጎት እያስተናገደ መሆኑን የሰሜን ምዕራብ ሪጅን ትራንስሚሽንና ሰብስቴሽን ኦፕሬሽንና ጥገና መምሪያ አስታወቀ፡፡

የመምሪያው ዳይሬክተር አቶ ውበት አቤ እንደገለፁት በሪጅኑ የኃይል ፍላጎት በከፍተኛ ፍጥነት እያደገ ቢመጣም አሁን ላይ ጥያቄውን ለመመለስ አስቸጋሪ አልሆነም፡፡

ይሁንና በወረታ፣ በእንጅባራና በቡሬ ከተሞችና አካባቢያቸው እየመጣ ያለውን ተጨማሪ የኃይል ፍላጎት ማስተናገድ የማይቻልበት ሁኔታ ተፈጥሯል፤ በወረታ ከተማና አካባቢው ኤሌክትሪክ በፈረቃ ማዳረስ ተጀምሯል ብለዋል፡፡

በቡሬና ደብረማርቆስ ግንባታቸው የተጀመሩት ማከፋፈያ ጣቢያዎችና በደብረታቦር ሊገነባ የታቀደው የማከፋፈያ ጣቢያ አሁን ያለውንና ወደፊት ሊመጣ የሚችለውን ጥያቄ ለመመለስ እንደሚያስችል አቶ ውበት ተስፋቸውን ገልፀዋል፡፡

የባህርዳር 2 ማከፋፈያ ጣቢያ ኃላፊ አቶ ዮሐንስ ዕድሉ በበኩላቸው 45 ሜጋ ቮልት አምፒር አቅም ካለውና እስከ 40 ሜጋ ዋት መሸከም ከሚችለው የደብረታቦር ተንቀሳቃሽ ማከፋፈያ ጣቢያ ከተማዋ፣ ዪኒቨርሲቲውና አካባቢው  እየተጠቀመ ያለው 10 ሜጋ ዋት እንደማይደርስ አስታውቀዋል፡፡

በመሆኑም ቀደም ሲል በወረታ በኩል ደብረታቦር ኃይል ሲያገኝበት በነበረው የሥርጭት መስመር ወረታና አዲስ ዘመን ከተሞች ተጨማሪ ኃይል የሚያገኙበት ዕድል ስላለ ሊታሰብበት ይገባል፡፡

በባህርዳር 2 ካለው ማከፋፈያ ጣቢያ የመከላከያ ስርዓት መቆጣጠሪያ እና ዳታ ከመቆጣጠሪያው ወስዶ ትዕዛዝ በሚሰጠው (Relay) ላይ መጠነኛ ጥገና በማድረግ ለባህር ዳር ከተማ ተጨማሪ ኃይል መስጠት የሚችሉ 3 ባለ 15 ሺህ ቮልት መስመሮች ዝግጁ ማድረግ ይቻላል፡፡

Categories: ዜና

0 Comments

Leave a Reply

Avatar placeholder

Your email address will not be published.

4 × four =