የዋና ሥራ አስፈጻሚ መልዕክት

ኢትዮጵያ ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት ፈጣንና ተከታታይ ሁለንተናዊ ዕድገት ማስመዝገብ ችላለች፡፡

ለእነዚህ የልማት ትሩፋቶች የኤሌክትሪክ ኃይል የማይተካ ሚና ተጫውቷል፡፡

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል እንደ አዲስ ከተቋቋመ ዘጠኝ ዓመታት ያስቆጠረ መ/ቤት ሲሆን፤ በእነዚህ ዓመታት ውስጥም በርካታ ሥራዎችን ማከናወን ችሏል፡፡

በተለይም ተቋሙ እንዲያከናውን በአዋጅ ከተሰጡት አበይት ተልዕኮዎች መካከል የኃይል ማመንጫዎች ግንባታ ዋነኛ ተግባሩ ሲሆን በዚህ ረገድም ከውሃ፣ ከንፋስ፣ ከደረቅ ቆሻሻ እና ከከርሰ ምድር እንፋሎት (ጂኦተርማል) የኃይል አማራጮች የተለያዩ የኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶችን በመገንባት ላይ ይገኛል፡፡

ከእነዚህ የኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶች መካከልም በ2009 ዓ.ም. በይፋ ተመርቆ አገልግሎት መስጠት የጀመረው የጊቤ III የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫን ጨምሮ፡-

የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ፕሮጀክት ሥራ 86.94 በመቶ
የኮይሻ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት 52.85 በመቶ የተከናወኑ ሲሆን
ባለ 500 ኪሎ ቮልት የኢትዮ – ኬንያ እና ባለ 400 ኪሎ ቮልት የገናሌ ዳዋ III ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ኃይል ማስተላለፊያ መስመሮች ግንባታ ተጠናቀው አገልግሎት መስጠት ጀምረዋል፡፡

እንዲሁም የሚመነጨውን የኤሌክትሪክ ኃይል ወደ ብሔራዊ የኃይል ቋት እንዲገባ በማገዝ ረገድ ጉልህ ድርሻ ያላቸውን በርካታ ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ኃይል ማስተላለፊያ መስመሮች እና የኃይል ማከፋፈያ ፕሮጀክቶች በመገንባት ላይ ይገኛሉ፡፡

የሀገሪቱን የኃይል ፍላጎት ከማሟላት ጎን ለጎን ከፍጆታ የሚተርፈውን የኤሌክትሪክ ኃይል ለውጭ ገበያ በማቅረብ የማይናቅ የውጭ ምንዛሪ ማስገኘት ከማስቻሉም በላይ አህጉራዊ የምጣኔ ሀብት ትስስር የተሻለ እንዲሆን የሚያደርገውን አስተዋፅኦ ያሳድገዋል፡፡

እነዚህንና ሌሎች በርካታ ተግባራትን በማከናወን ተቋማችን የኤሌክትሪክ አቅርቦትን ለማሳደግ የያዘውን ግብ ከፍተኛ በሚባል ደረጃ ማሳካት ችሏል፡፡ በመሆኑም ተቋማችን የተጀመሩና ያልተጠናቀቁትን ተግባራት በተሻለ መንገድ እንዲፈፀሙ በማድረግ በአሁኑ ጊዜ ያለውን 5,200 ሜጋ ዋት ኃይል የማመንጨት አቅም ለማሳደግ ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡

በተለይም በኃይል ልማቱ ዘርፍ የሀገር ውስጥም ሆኑ የውጭ ባለሀብቶች ከመንግስት እና ከግሉ ባለሀብት ጋር በሽርክና በጋራ መስራት የሚችሉበትን (Public private partnership) መደላድል፣ ፖሊሲ እና የህግ ማዕቀፎች ተዘጋጅተው በሚኒስትሮች ምክር ቤት እና ተወካዮች ምክር ቤት ፀድቀው ሥራ ላይ እንዲውሉ ተደርጓል፡፡

በመሆኑም ይህ የአሰራር ሥርዓት ተግባራዊ እንዲሆን መደረጉ ለኃይል ልማት ዘርፍ ተጨማሪ አቅም ከመፍጠሩም በላይ የሀገር እና የውጭ ሀገር አልሚዎች በጋራ የዳበረና የበለፀገ ዕውቀት እና የቴክኖሎጂ ሽግግር ለማድረግ እንደሚግዝ ይታመናል፡፡

በዚህም መሰረት በመንግስትና የግል አጋርነት (መግአ) ቦርድ አስራ ሶስት የኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶች የተመረጡ ሲሆን ከአስራ ሶስቱ ውስጥ ስድስት የሶላር ፕሮጀክቶች ወደ ጨረታ እንዲገቡ ውሳኔ አግኝተዋል፡፡ ቀሪዎችም በተመሳሳይ መልኩ ለመግአ ቦርድ እየቀረቡ የሚፀድቁ ይሆናል፡፡

በቀጣይም ለንፋስ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶች ልማት የሚያስፈልጉ ዝርዝር ጥናቶች በማካሄድ በቂ የንፋስ ኃይል የሚገኝባቸውን ሥራዎች የመለየት፣ የቅኝት እና ቅድመ ጥናቶች (Reconnaissance and feasibility studies) እንዲሁም የጨረታ ሰነዶች ዝግጅት ሥራዎች በመከናወን ላይ ናቸው፡፡

ስለሆነም ይህንን ሰፊ ዕቅድ ከግብ ለማድረስ ሁሉም የተቋሙ አመራሮችና ሠራተኞች ተቋሙ የሚፈልገውን የኮርፖሬት ቢዝነስ አስተሳሰብ መላበስና ዘመናዊ አሰራር በመዘርጋት፣ በቀጣይነት የሚማርና የሚያድግ ተቋም ለመገንባት እጅ ለእጅ ተያይዘን ከፍተኛ ርብርብ ማድረግ እንደሚጠበቅብን ለማስገንዘብ እወዳለሁ፡፡